Skip to main content

Posts

Showing posts from 2013

ስትሄጅ አትንገሪኝ

ምንም አትበይኝ፣ ስትሄጂ ጥለሺኝ ዝም ብለሽ ሂጂ፣ መሄድሽን ሳትነግሪኝ፤ ከኔጋር ለመሆን፣ ልብሽ ባይፈቅድልሽ መንገዱ ግን ይቅናሽ፣ ክፋም አይግጠምሽ፤ ፍቅርሽን መሸከም፣ ጫንቃዬ ባይችልም ከኔ ጋር ሁኚ፣ ብዬ አላስገዽሽም:: መሳቅ ሲያስፋልገኝ፣ በትዝታ አይሻለሁ ማልቀስ ቢያስፈልገኝ፣ ብቻዬን ቁጭብዬ እነፈርቃለሁ፤ በቃ በቃ ሂጂ፣ ዞር ብለሽ አትይኝ ሆዴን አታባቢው፣ ቻዎም አትበይኝ፤ ድምዕሽን አጥፊና፣ ኮቴሽን ጠብቀሽ ሳታንኮሻኩሺ፣ ውጪ ልቤን ዘግተሽ ቁልፉን ግን አስቀምጪው፣ አደራ ይሁንብሽ፡፡ ታዬ አለሙ 2005 ዓም ትንሽ ማስተካከያ ›› በአኒቲ

እናት - ያው - እናት - ናት!

በዚህ በኩል -  ህጉን ጣስሽ ብሎ፣ ያመናጭቃታል የደኑ ጥበቃ፣ ይተናኮላታል ፣   ሊያስር ያሳዳታል ሸክሟን ያስጥላታል፣ በባዶ ይሰዳታል ለእሷ ምግቧ ነው፣ ጉርሷ ይጨንቃታል፤ እውነት ለመናገር፣ አሷስ መቼ ጨንቋት ከእሷም ጉርስ በላይ፣ አለ ሚያሳስባት እንዲ አስጠግርሮ፣ ወገቧን ሚቆርጣት የሀረጓ ቅጣያ፣ የማህፀኗ ክፋይ ፣ የይሆናል እዠት መቼስ ገመተና? ይችል እንደሆነ፣ አንድ እንኳ ሊኖራት፤ ሲርበው የሚያለቅስ፣ ሲጠግብ የሚቧረቅ፣ ሄኔ ያስተኛችው ማንያውቃል ይኖራት ይሆናል፣ ባለማወቅ ብቻ፣ ብዙ የወለደቸው ተርቦ ሚገባ፣ ይማርልኝ ብላ፣ ትምህርት የላከቸው፡፡ ተሸክማ ደክማ፣ ጎብጣና ገርጥታ፣ ሆና ያልተሻለች ከዛሬ ህይወቷ፣ የተሸለ እንዲኖር፣ ለልጇ የተመኘች ፤ አመጣጡን ያውቃል፣ ጠንክሮ ይማራል ከግቡ ላይ ደርሶ፣ ላቤን ይጠርገዋል ፤ ምን ያደርጋል ታድያ፣ በሕልም ዓለም ስትስል ተጨናገፎ ቢቀር፣ የልቧን ሣያክል:: ዛሬን እንዳረጀች፣ የጇን መች አገኘች ህልሟ መች ተሳካ፣ መች ምኞቷን ኖረች ከአሁን ቡሀላ፣ መችስ ትኖራለች፤ ተስፋዬ ያለችው ገና ነፍሱን ሳያውቅ፣ ሱስ ቀድሞ እያወቀ ጠንክሮ እንደመስራት፣ በወሬ እየሞቀ፤ ላይብረሪ እያለ፣ ፑል-ቤት ሄዶ መዋል አዳር ላጥና ብሎ፣ በጭፈራው መጋል ከማይሆኑ ገጥሞ፣ እነሱን ለመምሠል፤ ልፋቷን በትኖት፣ ዋልጌ ሆኖ ቀረ፣ ገና በ ሀይ-እስኩል፡፡ ከወገቧ ጉብጠት፣ ከሸክሟም ክብደት ልቧ እንዳይሠበር፣ ሁሉም ፍቅር ይስጣት የኛ እናት ባትሆንም፣ በሠፈር ካወቅን፣ እንደዚህ ያለች ሴት ብቻዋን እንዳቱል፣ ሄደን እናጫውታት፣ ካለንም እንርዳት በዓልም ሲደርስ፣ እንሂድ እናፅናናት፣ እንደ ልጅ እንሁናት ቸ...

እየኖሩ ሞት

ሠምተን ስትሠቃይ፣ ከነጎድን ትተናት እየቻልን ማቅናት፣ ከጎን ቆመንላት በግዴለሽነት፣ ረጋግጠን ካለፍናት ትርጉሟ በተግባር፣ መስጠት ከሌለባት መኖር ምን መኖር ናት? ለራስ እየበሉ፣ ሌላ ተርቦባት ለራስ ተጋጊጠው፣ ይሄ ታርዞባት ቤቤት ተጠልለው፣ ተርፎ እያከራ ዩ ት፤ በራስ መውደድ ጠኔ፣ በየቁም ድንዝዛት ሲያድር ሠው ትቦ ውስጥ፣ አይተው እንዳላዩት ሢያስል በክረምቱ፣ ሠምተው እንዳልሠማት:: እንኳን እና ገንዘብ፣ ወይን የቁስ ንብረት መች የማያስከፍል፣ የልብ ፍቅር ሠጡት ቆሻሻ እያረጉት፣ ነጣቂ  ነው አሉት ምክንያቱን ሳያያዩት፣ ቀርበው ሳይረዱት የአደም ልጅ መሆኑን፣ እያወቁ ሳቱት፡፡ መኖር ሳትሆን ይቺህ፣ የማይሠጥ ሠው ህይወት ያለምንም ለቅሶ፣ ያለአንዳች ግንዛት እየተነፈሱ እየተራመዱ፣ እያካበቱባት ሀፍት እየታዩ እያሉ፣ እየኖሩ ሞት ናት፡፡ ሐምኔ 15፣ 2005 © አኒቲ 

በብሄራዊ ቡድኑ መቀጣት የተነሣ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ባጃጆች የሥራ ማቆም አድማ ሊያደርጉ ነው፡፡

ኢትዮጵያ ከደቡብ አፍሪቃ ባስመዘገበችው የዓለም ዋንጫ ማጣርያ ማሸነፍ ምክንያት ህዝቡ ሲያደርገው በነበርው ሀገር አቀፍ የፈንጠዝያ ዱብእዳ በተለያዩ የሀገሪቷ ትልልቅ ከተሞች (ማለትም መቀሌ፤ ባሕር ዳር፤ አዳማ፤ ሐዋሳ እና ሌሎችም) ውስጥ የሚኖሮ፣ ህንድ ሠራሽ ኢትዮጵያ ነዳሽ ባጃጆች ላያ ይህ ነው የማይባል የሰብዓዊ መብት ረገጣ በማከናወናቸው ምክንያት፣ በዛሬው እለት ባጃጆቹ ተወካዮቻቸውን መርጠው አዲስ አበባ ወደሚገኘው የህንድ ኢንባሲ መላካቸው ተገለፀ፡፡ የውስጥ ምንጮች ለዜና አውታራችን እንዳስረዱት ከሆነ፣ ጉዳዩን እስከዛሬ ችላ ብለው የቆዩት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እውነትም ለማጣሪያው አንድ ቀሪ ጫወታ እያለው በቀጥታ ማለፉን በመስማታችን እና በመስማማታችን ነው፣ ሲሉ ነገር ግን ለዛሬው አቤቱታ ያበቃቸውን ነገር ከመቀሌ የተመረጡት ህንድ ሠራሽ ሀበሻ ነዳሽ ታርጋ ቁጥራቸው  ኮድ 1   መ ቀ- 2334  የሆነው ባጃጅ እንዳሉት፤ “ሁለት ምክንያት  ለዚህ አቤቱታ እዚህ አዲስ አበባ ወደሚገኘው ሀገራችን የህንድ ኢንባሲ አምጥቶናል:: አንደኛው ነገር እኛ ለዚህች ሀገር እንሥራ እንጂ ዜጋዋ አይደለንም፣ ዜጋዋ ብንሆን ኖሮ እንዲህ ያለ ከፍተኛ ጉዳት እና ከፍተኛ የሞራል ውድቀት በራሳችን ወገን አይደርስብንም ነበር፤ ሆኖም ግን በሠው ሀገር እንደመሆናችን እና በተገኘው ውጤት የምናገለግለው ህዝብ ምንም ቢረግጠንም ተደስቶ ማየታችን ጥሩ ሆኖ ሳለ እስከዛሬም ዝም ብለን ችለን ዛሬ ግን ነጥብ መቀነሱን በመስማታችን እኛም እንዲህ ላለ ከንቱ ጉስቁልና መዳረጋችን ስላሳዘነን ነው አቤት ለማለት የመጣነው”  በማለት የተሠማቸውን ሀዘን ድብልቅልቅ ባለ ስሜት ገልፀውልናል፡፡ በሌላ በኩል ከሐዋሳ ተወክለው የመጡትን ታ...

የፈጠራ ሥራ ውድድር ማስታወቅያ

የኢትዮጵያ የኬሚስት ባለሞያዎች ማህበር በሀገሪቷ እድገት ውስጥ ያለውን ሚና ከፍ ለማድረግ፤ እነደ መቋቋሙ መጠን አስካሁን ተጨባጫ የሆነ ተግባርን ሳያከናውን ቆይቷል፡፡  ሆኖም ግን ሀገራችን እያስመዘገበች ያለው እድገት፣ ተነሳሽነታችንን በእጅጉ እንደሚያነቃቃ በማመን፣ ማህበሩ ለውድድርነት ይሁን ዘንድ ይህንን የመወዳደሪያ ዘርፍ ለመጀመርያ ግዜ ማስለፈፍ አስፈልጓል፡፡ ተፈላጊ ችሎታ፡- በኬሚስትሪ ወይም በኬሚካል ኢንጂነሪንግ ከታወቀም ወይም ካልታወቀም ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ወይም የመጨረሻ  ዲግሪ ያለው ወይም ያላት፡፡ የመወዳደሪያ ዘርፍ፡- ሀገር በቀል አረቄ፡፡ የውድድሩ አስፈላጊነት፣ ግብ እና አላማ፡- የሚከተሉት አምስት ነጥቦች ለውድድሩ አስፈላጊነት እንዲሁም የትግበራው የረጅም እና የአጭር ግዜ ግብ እና አላማዎች ናቸው፣ 1.       በ ሀገራችን ያሉ ኬሚስቶችን በፈጠራ ሥራ ላይ ማበረታታት፡፡ 2.      የሀገራችን ኬሚስቶች፣ በሀገር እድገት ውስጥ፣ (ከማስተማር እና ከመማር ባሻግር) ሊኖራቸው የሚገባውን ተጨባጭ ሚና፣ ማጠናከር፡፡ 3.      በፎርሙላ ማጣት ሳቢያ፣ አረቄ አውጪ ባልቴቶች፣ ለረዠም ግዜ ለኪሳራ እና ለስነልቦና ችግር እንደመጋለጣቸው መጠን፣  እስታንዳርዱን የጠበቀ የአረቄ ፎርሙላ በማውጣት በሀገር እኮኖሚ ላይ እየደረሰ ያለውን ውድመት መታደግ፡፡ 4.      ለኢትዮጵያ አረቄ አውጪዎች እና ቸርቻሪዎች ማህበር፣ ሳይንሳዊ ድጎማ በመስጠት አትራፊነታቸውን ማጠናከር እና በሀገር ...

ሲፈቀሩ ሽሽት፤ ሳያፈቅሩ ትዳር!

ፍቅርዬ ናት ብዬ፣ ያለውል የያዝኳት የውል ያለሆነችን፣ እኔም ሚስቴ ምላት ባሌ የምትለኝ፣ የውል ባል ያልሆንኳት ለሚቆጠር ዓመት፣ ከልቤ ያኖርኳት እሷም የምትወደኝ፣ እኔም የምወዳት ሽምቅቅ ያደርጋታል፤ ‘ ትዳር! ’ ብዬ ስላት፡፡                             በፍቅር መንደሬ፣ ከትማ ምትወደኝ ‘ እንጋባ! ’ ስላት፣ በመስፈርት ሸብባኝ፤ ውስጤ ቦታ-የሌላት፣ መጣች ያልተመራች በሥራ አጋጣሚ፣ ሦስቴ ከኔው የዋለች፤ በዛች ተብሰልስዬ፣ ብቀርባት በስንዝር በአንዴ ሠልላ፣ የውስጤን ለትዳር ግዜ ሳታባክን፣ ምንም ሳትፈቀር ብላኝ እርፍ አለች፣ ቀለበት እንሠር ፍየል እዚ. . . አልኩኝ፣ ዙሩ በጣም ሲከር፡፡ ለእኔዋ የታየኝ፣ እንደ እንቦሳ ጥጆች ጠብታ እንደጠገበች፣ ጠግባ እየቦረቀች ሳታውቅ በፍንጠዛ፣ ከደጇ እንደራቀች መሮጡም ሲደክማት፣ ሲመሻሽ ታውቃለች፤ አቁማ መቦረቅ ፣ ርቃ ለመመለስ፣ ብታዘግም ወዲ አይኖር ሚቀመስ፣ እናቷ ታልባለች፣ ተገዳ በጋዲ፡፡ እንደው የሠው ነገር፣ እኔንም ጨምሮ በጋርዮሽ ሕይወት፣ ለመኖር ተባብሮ በራስ መውደድ ጠኔ፣ ውስጣችን ተቋጥሮ፤ ሞልቶ የማይሞላን፣ አሸን ሺህ ፍላጎት፣ ስንከተል ላንደርስ ለሠው ሠው ካልኖረ፣ የሚፈላለግ ልብ፤ ጎጆን መች ይቀልስ? እሱ እሱን ሳስበው. . . ሠው እንደ ጉንዳን ነው፣ ኋላውን አያይም፣ የፊቱን ያፈቅራል ለትዳር ላይሆነው፣ የፊቱም የፊቱን፣ ዱካ ይከተላል፤ ሲመሽ በመጣደፍ፣ እንደ...

የድንቅነሽ/ሉሲ በደህና የመመለሷ ነገር . . .

ዛሬ ድንገት ኢቲቪ ተከፍቶ ዜና ሠማሁኝ እና ከዜናው አንዱ ትኩረቴን ሳብ አድርጎት ጆሮዬን ቀልቤን አቅሌን ሙሉ ለሙሉ ለኢቲቪ ሰጠሁ፡፡ ታድያሎ ያልኳችሁ ዜና እናንተም የሰማችሁት ያ ስለ ድንቅነሽ /ሉሲ/ ከ5 ዓመት ቆይታ ቡሀላ ከወደ አሜሪካን ሀገር ተመለሰች የሚለው ነበር፡፡ ገና የዜናው ርዕስ እንደሰማሁኝ ነበር፤ እንኳን በደህና ሄደሽ ባልልም፤ እንኳን ደህና መጣሽ ማለቴ ግድ ነበር፤   እናም አልኩኝ፡፡ ሙሉ የዜናውን ሀተታ እና የምስል ቅንብር ስመለከት፤ለርክክቡም አሜሪካዊ እና ታዋቂ ብሎም አዋቂ የኢትዮጰያዊ ተመራማሪዎች ከአሜሪካን ድረስ እዚህ መገኘታቸውን ሠማሁ፡፡ ከዛማ እንኳን በደህና ተመለስሽ ያልኩት አባባል ግልፅነት እና ተጠያቂነት የጎደለው ደብዛዛ ምስክርነት መስሎ ታየኝ፤ ጥርጣሬም ወረረኝ፡፡ ለምን እና እንዴት ካላችሁ. . . . . የ እኛ ምሁራን ሉሲን ገቢ ያደረጉበት የማረጋገጫ መለኪያ ተጠቀምን ያሉት ስልት እንደ ስለት አሳቀቀኝ፡፡ ፕሮፌሰሩ ቃል ሲሰጡ፤ “እያንዳንዷን አጥንት መዝነን፣ ለክተን ነው የተቀበልነው::” በዜናው ላይ የቀረበው የ ርክክብ ቪዲዮ ላይ እንዳየነው፤  እና መገለጫችን የሆነውን የሉሲን አፅም ለዛውም ለ5 ዓመት ያህል ሠው ቤት ቆይቶ እንደሚመለስ ብርቅዬ ቁስ ሳይሆን እንደ አሞሌ ሲቀባበሉ መመልከቴ አስገርሞኛል፡፡ በተለይ በተለይ የእኛው ምሁራን ይህችን በስንት ምርምር የእድሜ ጠገብነቷን ሚስጢር በዓለም አቀፍ ደረጃ ለመለየት ብዙ ምርምር የተደረገላትን በክብደት እና ቁመት በመለካት ማረጋገጥ ችለናል ማለታቸው አግራሞት ፈጥሮብኛል፡፡ እኔ የምለው እንደው ደረጃ መዳቢዎች ባለስልጣን እራሱ ዘይትን ከውጪ ለማስገባት ምን ያህል የላብራቶሪ ፍተሸ እናደሚያካሂድ ባለፈው ዘይት እንትን ያ...

በህዳሴው ግድብ ስም አስገራሚ ማጭበርበር

ሰሞኑን የወዳጄ ወዳጅ ከምሽቱ ሦስት ሠዓት ተኩል አከባቢ አንድ የስልክ ጥሪ ያስተናግዳል፡፡  ከበስተማዶ ያለው ደዋይ ድምፅ ሆነ ንግግር ቅልጥ ካለ የአየር ላይ የሬዲዮን ውይይት ይመስላል፡፡ መሆኑም አልቀረ በጣም ብዙ ልምድ ያለው ጋዜጠኛ የሚመስለው ግለሰብ ጎርነን ባለ ድምፅ  ‹‹ከኤፍ ኤም ነው ጤና ይስጥልኝ›› ብሎ ሠላምታውን ያቀርብለታል፡፡ የወዳጄ ወዳጅ ከማያውቀው የስልክ ጥሪ ባገኘው ሞቅ ያለ ሠላምታ ድንግርግር እያለ ፈጣሪን በማመስገን ምላሹን በሠላምታ ሠጠው፡፡ ከስልኩ ወድያ ማዶ ያለው ጋዜጠኛው ደዋይ ቀጥሏል   ‹‹…….. ይህ አዲስ የሬድዮ ፕሮግራም ዜጎች ለህዳሴው ግድብ ግንባታ ያላቸውን ርብርብ በዘለቄታው ለማነሳሳት እና በግድቡ ዙርያ ያላቸውን እውቀት ለማጠናከር በማሰብ የተዘጋጀ ነው፡፡ ፕሮግራሙ በታዋቂው የሀገራችን ባለሀብት አቶ (እከሌ) ድርጅቶች አማካኝነት እስፖንሰር የተደረገ ሲሆን የተለያዩ የሀገራችን ዜጎች ስልክ ላይ በመደወል ስለ ህዳሴው ግድብ አስመልክቶ 3(ሶስት) ጥያቄዎችን የምንጠይቅ ሲሆን ለሶስቱም ጥያቄዎች ሙሉ ምላሽ ለመለሱ የ 5000 (አምስት ሺህ) ብር ሽልማት አቅራቢያው በሚገኝ ባንክ አማካኝነት በመላሹ ስም ወይም በአካውንት ቁጥሩ እናስተላልፋለን፡፡››  በማለት ጠቅላላ አላማውን እና ሂደቶቹን በአጭሩ አስቀመጠለት፡፡ እናላችሁ የወዳጄ ወዳጅ የሠማውን ማመን እያቃተው፣ አረንጓዴው የመቶ መቶ የብር ረብጣ በፊቱ ውልብ እያለ፣ እድለኛነቱን በውስጡ እያደነቀ፣ መጓጓቱን በሚያሳብቅ ድምፅ  ‹‹ … እሺ አመሰግናለሁ ጠይቁኝ … (መግደርደሩን ለመግለፅ እና መጓጓቱን ላለማሳወቅ) እሞክራለሁ›› በማለት ለኤፍ.ኤም. ጋዜጠኛ ነኝ ባዩ ደዋይ የንግግሩን ቀጣይነት የ...