የባጡን የቆጡን ማህላ እየማልኩልሽ
ልሰቀል ነው ልሞት ብዬ ጎተጎትኩሽ
ልብሽን ሸርሽሬ የእኔ የብቻዬ ትሆኝ ዘንድ አረግኩሽ፤
የት ይደርሳል ሲባል አይን ውስጥ ገባሁና
እንደ በሬው ሆንኩኝ ቄራ ታየሁና፡፡
አንቺ እያለምሽኝ ያገባኛል ብለሽ ሳላገባሽ ቀረሁ
መጥፎሽን አግዝፌ ቀስ ብዬ ሸሸሁ
ጥሩሽን ሸሽጌ ገላ ጠረንሽን አሽቼ ብጠግበው፤
እውነት ለመናገር
ዛሬ ላይ ቁጭብዬ ትላንትን ስለካ
‘በእጅ-ያለ-ወርቅ …..’ እንዳሉት፣ ውስጤ ይፀፅታል
በሚዘው አይረካ፡፡
እስካሁን ብቆይም፣ ደብቄሽ ስሜቴን፣ አልሸነፍ ብዬ
ሲያይሽ ልቤ
እንደ አዲስ፣ ወጥተሽ ከጉያዬ፤
እንዳልሆነ ምንም፣ አንቺን ሲመለከት
የሚያደርገው ነገር፣ እንደሆነ ውሸት፤
በእናቴ ምላለው፣ እየታገለው እንጂ፣ የልቡን መፀፀት
ፊቴ-ይናፍቀዋል፣ ፊቴ ያስፈልገዋል፣ የያኔው ፈገግታ
የያን ግዜው ስሜት፡፡
እውነት የኔ ፍቅር፣ እውነት ለመናገር
ያዛኔን ሽርሽር የየያኔ ገላሽን፣ ለሊት እንኳ
ሳይቀር፤
ቀንማ ምንላድርግ፣ አምረሽ እያየሁሽ ፈርቼ ተዋለሁ
ለሊት ማን ከልክሎኝ፣ እኮመኩማለሁ
የያኔው አልበሜን፣ ላይሽ ከፎቶዬ፣ እንደከሰረ ዓረብ
አገላብጣለሁ፡፡
ዓይኔን በጨው ባጥብም፣ ባይሠማኝ ዩሉኝታ
እድል ስጪኝ ውዴ፣ እስኪ ለአንድ ላፍታ፤
ልቤ ልብ ገዝቶ፣ ለመመራት መቷል፣ የይቅርታን
ቦታ
አጢኚው ደጋግመሽ፣ ይህን አቤቱታ፡፡
ገንፍሎ ሲያገረሽ ፣ ሆንሽና ስራዬ
መጣሁ ያንቺ ጠላት፣ ሁለቴ ልማረክ፣ እጅ ወደላይ
ብዬ
ነጠላ አዘቅዝቄ፣ ቅንድቤን ላጭቼ፣ እያለቃቀስኩኝ
ውስጥሽን ገድዬ፤
ከደሙ እንደነፃ፣ ለቅሶው ላይ ያቆመኝ
ምክንያቱን እወቂ፣ በዳግመ-መውደድሽ፣በዳግመኛው-ፍቅርሽ፣ አቅሌን ስላጣሁኝ፤
እንደ እጣ ወጥቼ፣ እጅሽ ገብቻለሁ
ያረግሽኝን አድርጊኝ ፈቅጄልሻለሁ፤
ስትፈልጊ ብይኝ፣ አልያም እንዳሻሽ፣ ዘልዝለሽ ስቀይኝ
ግን ከልብሽ ጓዲያ፣ ከወጠርሽው ገመድ፣ ዘርግተሸ አድርቂኝ፤
ይቅር ብለሽ በይኝ!!
© በአኒቲ/by Aniti
ጥቅምት፣ 2005/Nov, 2012

Comments
Post a Comment